Tuesday, February 15, 2011

“አእምሩ ከመ ተሰብሐ እግዚአብሔር በጻድቁ፤ እግዚአብሔር በጻድቁ እንደተገለጠ እወቁ።” (መዝ. 4፥3)

የብፁዕ አባታችንን የአቡነ ዜና ማርቆስን እረፍት ምክንያት በማድረግ በነጸብራቅ መጽሔት ልዩ እትም ላይ ባለፈው ዓመት ከወጡ ጽሑፎች

የቅዱሳን ጻድቃን ሕይወት በፍጹም ሃይማኖት ተመሥርቶ በቅድስና ለእግዚአብሔር የተሰጠ በመሆኑ አምላካቸው እግዚአብሔርም ልዩ ሥራውን የሠራበት፣ ኃይሉን ያሳየበት፣ በረከቱን ያስተላለፈበትና ክብሩንም የገለጠበት ታላቅ ሕይወት መሆኑን መጻሕፍት አምላካውያት በመተባበር ይመሰክራሉ። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳን ሕይወት በዝቶ የተትረፈረፈውን ይህን አምላካዊ ጸጋ ሲገልጡም “ሰብእ ይቄድሶ ለመካን፥ ወመካን ይቄድሶ ለሰብእ፤ ሰው ቦታን ይቀድሳል፣ ያከብራል፥ ቦታም ሰውን ይቀድሳል፣ ያከብራልም” ብለዋል። በዚህም ቃል መሠረት መላ ሕይወታቸውን ለመንፈሳዊ አገልግሎት የሰጡት ታላቁ ኦርቶዶክሳዊ የበረከትና የትሩፋት አባት ብፁዕ አባታችን አቡነ ዜና ማርቆስ የረገጡት ቦታ ተቀድሶና ከብሮ፣ የጨበጡት ሁሉ ተባርኮ፣ የተናገሩት ቃል ተሰምቶ እግዚአብሔር ሥራቸውን ፍጹም ስለባረከላቸው የሲያትል መካነ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤልን ፍጹም አከበረው። በመሆኑም በኢትዮጵያውያን ኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ሲያትል የሚታወቀው በቦይንግ ወይም በማይክሮሶፍት ማዕከልነቱ መሆኑ ቀርቶ በታላቁ ሐዋርያ በብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ሀገረ ስብከትነቱ ሆነ። 

ዓመት እንደ ዋዛ


ዓመት እንደ ዋዛ

የቅዱስ ሲኖዶስ
ክብር ግርማ ሞገስ
ጻድቅ ዜና ማርቆስ
ባርኩን በአጸደ ነፍስ።
      
ቀን ሲቆጠር ጊዜ
የመሮጡ አባዜ
ግባ መሬት ምሡ
አፈርን ሳይቀምሱ።

ሳምንት ሁለት ሳምንት ወራት እየበዛ
ያሉ እየመሰለን ዓመት እንደ ዋዛ።
ከእኛ ጋራ ሆነው ዘውትር ስናያቸው
አብረን ውለን አድረን ከቶ ማን ጠግቧቸው።
           
ቅዱስ አባታችን የተዋሕዶ ቤዛ
ዜና ከተለዩን ዓመት እንደዋዛ።
ብሩህ ገጽታዎን ሳናየው ብንቀር
እናት እንደ ሞተው ብሎናል ቅር ቅር።

ሺህ ዓመት ቢቆጠር ፍቅርን ድል አይነሳም
ዜና አባታችንን ምን ጊዜም አንረሳም።
እውነተኛ ባርያ ለጌታ የተገዛ
በቅፉ ካፈሩ ዓመት እንደዋዛ።

ከልጃቸው ከሰባኬ ወንጌል ሽመልስ ተሊላ